በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

3ኛው ቁልፍ፦ ተባብሮ መሥራት

3ኛው ቁልፍ፦ ተባብሮ መሥራት

3ኛው ቁልፍ፦ ተባብሮ መሥራት

“ከአንድ፣ ሁለት መሆን ይሻላል፤ አንዱ ቢወድቅ፣ ባልንጀራው ደግፎ ያነሣዋል።”—መክብብ 4:9, 10

ምን ማለት ነው? የተሳካ ትዳር ያላቸው ባልና ሚስት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሰፈረውን አምላክ የሰጠውን የራስነት ሥርዓት ያከብራሉ። (ኤፌሶን 5:22-24) ያም ሆኖ ባልም ሆነ ሚስት ትዳራቸው የተሳካ የሚሆነው በግላቸው በሚያደርጉት ጥረት ሳይሆን ተባብረው በመሥራታቸው መሆኑን ያውቃሉ። ባልና ሚስት ተባብረው የሚሠሩ ከሆነ እንዳላገባ ሰው አያስቡም። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገረው “አንድ ሥጋ” ናቸው፤ ይህ መግለጫ የጋብቻው ጥምረት ዘላቂ መሆኑን ብቻ ሳይሆን በመካከላቸው የጠበቀ ቅርርብ እንዳለም ያመለክታል።—ዘፍጥረት 2:24

አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው? አንተና የትዳር ጓደኛህ ተባብራችሁ የማትሠሩ ከሆነ ጥቃቅን የሆኑ ነገሮችም እንኳ በአጭር ጊዜ ውስጥ ትልቅ ችግር ይሆኑና ችግሩን መፍታት ትታችሁ አንዳችሁ በሌላው ጉድለት ላይ እንድታነጣጥሩ ያደርጓችኋል። በአንጻሩ ደግሞ ተባብራችሁ የምትሠሩ ከሆነ፣ ከተቃራኒ አቅጣጫ እንደሚመጡ ሁለት የአውሮፕላን አብራሪዎች ሳይሆን የጋራ የበረራ እቅድ እንዳላቸው የአውሮፕላን አብራሪና ረዳቱ ትሆናላችሁ። በማትስማሙበት ጊዜም አንዳችሁ ሌላውን ጥፋተኛ በማድረግና በመወቃቀስ ጊዜና ጉልበት ከማባከን ይልቅ ተግባራዊ የሆኑ መፍትሔዎችን ትፈልጋላችሁ።

ይህን ለማድረግ ሞክር፦ ለሚከተሉት ጥያቄዎች መልስ በመስጠት ተባብሮ ስለመሥራት ያለህን ስሜት ገምግም።

የማገኘውን ገንዘብ ሠርቼ ያመጣሁት እኔ ስለሆንኩ ብቻ “የእኔ ብቻ” እንደሆነ አድርጌ እመለከተዋለሁ?

የትዳር ጓደኛዬ ከዘመዶቿ ጋር የምትቀራረብ ቢሆንም እኔ ከእነሱ ለመራቅ እሞክራለሁ?

በደንብ ዘና ለማለት ስፈልግ ከትዳር ጓደኛዬ መራቅ እንዳለብኝ ይሰማኛል?

ቁርጥ ውሳኔ አድርግ። ከትዳር ጓደኛህ ጋር ተባብረህ እንደምትሠራ ይበልጥ ማሳየት የምትችልባቸውን አንድ ወይም ሁለት መንገዶች አስብ።

አንድን ጉዳይ በሚመለከት የትዳር ጓደኛህ ምን ሐሳብ እንዳላት ለምን አትጠይቃትም?

[በገጽ 5 ላይ የሚገኝ ሥዕል]

ተባብሮ መሥራት ሲባል የጋራ የበረራ እቅድ እንዳላቸው የአውሮፕላን አብራሪና ረዳቱ መሆን ማለት ነው